የኢትዮጵያ አክሬዲቴሽን አገልግሎት (EAS) የሀገሪቱን የአክሬዲቴሽን ሥርዓት በዓለም አቀፍ ደረጃ ይበልጥ ተወዳዳሪና ተቀባይነት ያለው ለማድረግ የሚያከናውነውን ጉዞ የሚያጠናክር አዲስ ስኬት አስመዝግቧል። ተቋሙ ከግሎባል አክሬዲቴሽን ኮኦፕሬሽን (Global Accreditation Cooperation Incorporated – Global ACI) ጋር ያለውን የባለብዙ ወገን የጋራ እውቅና ስምምነት (Multilateral Recognition Arrangement – MRA) በይፋ በፊርማ ማደሱን አስታውቋል።
ይህንን ስምምነት የኢትዮጵያ አክሬዲቴሽን አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አቶ ቦንሳ ባይሳ ነገራ ግንቦት 14 ቀን 2018 ዓ.ም (May 22, 2026) በፊርማቸው ያረጋገጡት ሲሆን፣ የግሎባል ኤሲአይ ስምምነት ኮሚቴ ሰብሳቢ (Chair, Global ACI Arrangement Committee) ሚስተር ትሬስ ማክኢንተርፍ (Mr. Trace McInturff) በበኩላቸው ሚያዝያ 28 ቀን 2018 ዓ.ም (May 06, 2026) ፈርመውበታል።
ይህ የጋራ እውቅና ስምምነት የኢትዮጵያ አክሬዲቴሽን አገልግሎት በተለያዩ የስራ መስኮች የሰጣቸው አክሬዲቴሽኖች በዓለም አቀፍ ደረጃ ቀጣይነት ያለው እውቅና እንዲኖራቸው የሚያደርግ ሲሆን፣ በስምምነቱ የተካተቱት ዋና ዋና ዘርፎችና የተጀመሩባቸው ዓመታት የሚከተሉት ናቸው፦
- የላቦራቶሪ ምርመራ (Testing ISO/IEC 17025)፦ ጥቅምት 18 ቀን 2010 ዓ.ም (28 October 2017)
- የህክምና ላቦራቶሪ ምርመራ (Testing ISO 15189)፦ ጥቅምት 18 ቀን 2010 ዓ.ም (28 October 2017)
- የኢንስፔክሽን ስራዎች (Inspection ISO/IEC 17020)፦ ጥቅምት 13 ቀን 2012 ዓ.ም (23 October 2019)
- የካሊብሬሽን/የመለኪያ ላቦራቶሪ (Calibration ISO/IEC 17025)፦ የካቲት 6 ቀን 2016 ዓ.ም (13 February 2024)
- የአመራር ሥርዓት ሰርተፊኬሽን (Management System Certification ISO/IEC 17021-1)፦ ሰኔ 30 ቀን 2014 ዓ.ም (08 July 2022)
- የምርት ሰርተፊኬሽን (Product Certification ISO/IEC 17065)፦ የካቲት 4 ቀን 2016 ዓ.ም (12 February 2024)
ይህ ስምምነት መታደሱ የኢትዮጵያ ምርቶችና አገልግሎቶች የጥራት ደረጃቸውን ጠብቀው ያለምንም የቴክኒክ መሰናክል ወደ ዓለም አቀፍ ገበያ እንዲገቡ ትልቅ በር የሚከፍት ከመሆኑም በላይ፣ በሃገር ውስጥ የሚሰጡ የላቦራቶሪ፣ የኢንስፔክሽንና የሰርተፊኬሽን ውጤቶች በዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ዘንድ ያላቸውን አመኔታ ይበልጥ ያጠናክረዋል።
የኢትዮጵያ አክሬዲቴሽን አገልግሎት የሃገሪቱን ብሄራዊ የጥራት መሰረተ-ልማት ለማዘመንና የንግድ ዘርፉን በቀጥታ, መስፈርቶች ለመደገፍ የሚሰጠውን አገልግሎት አጠናክሮ እንደሚቀጥልም በዚህ አጋጣሚ ይገልጻል።

